
የእንጨት ውጤቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት መዘጋጀቱን የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ ገለጸ፡፡
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 28/2013 ዓ.ም (አሚኮ) ኢትዮጵያ የእንጨት ውጤቶችን በአብዛኛው ከቱርክ፣ ከቻይና፣ ከኢጣሊያ እና ከሌሎች የአውሮፓ እና ኤሲያ ሀገሮች ታስገባለች፡፡ ለዚህም ከ110 ሚሊዮን ዶላር በላይ በዓመት ወጭ ታደርጋለች፡፡
የአማራ ደን ኢንተርፕራዝም በክልሉ የደን ውጤቶችን እሴት ጨምሮ በማምረት ከውጭ የሚገባውን መተካት እና የውጭ ምንዛሬ አቅምን ማዳበር ካስቀበጣቸው ዓላማዎች መካከል አንዱ እንደሆነ የደን ኢንተርፕራይዝን ለማቋቋም በወጣ ደንብ ቁጥር 70/2002 ዓ.ም አስቀምጧል፡፡
ለዚህም በክልሉ አምስት የጣውላ መሰንጠቂያ ፋብሪካዎች በማምረት ላይ ይገኛሉ፤ ሦስት ፋብሪካዎች ደግሞ በግንባታ ላይ ናቸው፡፡
በመገንባት ላይ ከሚገኙት ፋብሪካዎች መካከል ደግሞ በላይ ጋይንት ወረዳ የንፋስ መውጫ የእንጨት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ አክሲዮን ማኅበር አንዱ ነው፡፡ የፕሮጀክቱ ሥራ አስኪያጅ ስዩም በላይ እንደገለጹልን የፋብሪካው መሠረተ ድንጋይ በ2009 ዓ.ም ተቀምጧል፣ በ2011 ዓ.ም የግንባታ ሥራው ተጀምሯል፡፡
ይሁን እንጅ በፕሮጀክቱ ላይ በተፈጠረው የዲዛይን ችግር፣ የኮሮናቫይረስ መከሰት፣ የዶላር እጥረት፣ በዚህ ዓመት ደግሞ የብረት አና የሲሚንቶ ዋጋ መጨመር ለግንባታው መጓተት በምክንያትነት አንስተዋል።
ፕሮጀክቱ በመጀመሪያ በነበረው የአዋጭነት ጥናት ላይ 140 ሚሊዮን ብር ይጨርሳል ተብሎ ቢጠበቅም በዚህ ወቅት ከዚያ በላይ እንደሚጨርስ ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ ለ120 ቋሚ እና እስከ 300 ለሚደርሱ ዜጎች ደግሞ በጊዜያዊነት የሥራ እድል ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ፋብሪካው በአካባቢው በስፋት የሚገኘውን ባሕርዛፍ በግብዓትነት እንደሚጠቀም ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡
ፋብሪካው ተገንብቶ ሲጠናቀቅ ለትልልቅ ግንባታዎች ማቀፊያነት የሚያገለግሉ ‹‹ፕለይ ውድ›› እና ‹‹ቬነር›› ጣውላ እንደሚያመርትም ተጠቅሷል። ከምርቱ የሚገኘውን እስከ 45 በመቶ ተረፈ ምርት ወደ ከሰልነት መቀየር የሚያስችል ፋብሪካ ያካተተ ነው።
ፋብሪካው በወረዳው ሰፋፊ ቦታ ላይ ያረፉ የመንግሥት ደኖችን ብቻ ሳይሆን በግለሰብ እጅ ያሉትንም በተሻለ ዋጋ በመረከብ በግብዓትነት ይጠቀማል።
ፋብሪካው እስከ ሐምሌ 30/2013 ዓ.ም ይጠናቀቃሉ ተብሎ ይጠበቃል። በ5 በጥብ 6 ሄክታር መሬት ላይም ያረፈ ነው።
የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ የደን ኢንዱስትሪ ዘርፍ ምክትል ዳይሬክተር መላኩ ጀምበሬ እንዳሉት ተቋሙ ከተቋቋመ 10 ዓመታትን ቢያስቆጥርም የእንጨት ውጤቶችን እሴት ጨምሮ በማምረት ከውጭ የሚገባውን መተካት እና የውጭ ምንዛሬ አቅምን ለማዳበር የተከናወነው ተግባር ዝቅተኛ ነው፡፡
በዚህም ባለፉት ዓምስት ዓመታት ለእንጨት ውጤቶች ይወጣ የነበረውን ገንዘብ ማዳን የተቻለው 21 ሚሊዮን ዶላር ብቻ መሆኑን በማሳያነት አንስተዋል፡፡
ፋብሪካዎች ለግብዓት የሚጠቀሙት የእድገት ዘመናቸውን የጨረሱ እንደ ጥድ እና ባሕርዛፍ የመሳሰሉ ገበያ ተኮር ደኖችን ነው፡፡ ለዚህም የዘር ባንክ እና የችግኝ ጣቢያዎችን በማዘጋጀት የተቆረጡ ደኖችን የመተካት ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝ ዳይሬክተሩ ገልጸውልናል፡፡
በደን ልማት፣ በዘር ማዕከል፣ በችግኝ ጣቢያዎች 1 ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ እና ጊዜያዊ የሥራ እድል ተፈጥሮላቸዋል ብለዋል፡፡ ተቋሙ ከደን ሽያጭ የሚያገኘው ገቢ 10 በመቶው ለአካባቢው ማሕበራዊ ልማት እንደሚውልም ነግረውናል፡፡
ዳይሬክተሩ እንዳሉት በቀጣይ ደንን በቁሙ ከመሸጥ ለመውጣት እና በኢንተርፕራይዞች እየተሠራ የሚገኘውን የጣውላ ሥራ ወደ ሁለተኛ፣ ሦስተኛ እና አራተኛ ደረጃ ምርቶች ማሳደግ ላይ ትኩረት ተደርጓል፡፡
ከውጭ የሚገባውን የዕንጨት ውጤት ማስቀረት ብቻ ሳይሆን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ማግኘት የሚያስችል የአስር ዓመት ዕቅድ በዝግጅት ላይ እንደሚገኝም አቶ መላኩ ነግረውናል፡፡ በዚህም በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ኤም.ዲ.ኤፍ. ምርቶችን ማምረት የሚያስችል ፋብሪካ መጠናቀቁን ለአብነት አንስተዋል፡፡
ዘጋቢ፦ ዳግማዊ ተሠራ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
The post የእንጨት ውጤቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት መዘጋጀቱን የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ ገለጸ፡፡ first appeared on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.