Quantcast
Channel: The Habesha: Latest Ethiopian News, Analysis and Articles
Viewing all articles
Browse latest Browse all 13041

በሲሚንቶ ግብይት የወጣውን የዋጋ ተመን ተግባራዊ ባላደረጉ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡

$
0
0


በሲሚንቶ ግብይት የወጣውን የዋጋ ተመን ተግባራዊ ባላደረጉ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን የአማራ ክልል
ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 28/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በአማራ ክልል የዋጋ ንረትን ለመከላከል ከመሠረታዊ የምግብ ፍጆታዎች
በተጨማሪ በሲሚንቶ ምርትም የዋጋ ተመን ወጥቶለት ተግባራዊ እየሆነ ነው፡፡ የተወሰነውን የዋጋ ተመን አተገባበር በተመለከተ
በባሕር ዳር ከተማ ተዘዋውረን ምልከታ አድርገናል፡፡ በዚህም አንዳንድ የሲሚንቶ መሸጫ ሱቆች መዘጋታቸውን፣ ምንም የሲሚንቶ
ምርቶችን ሳያስገቡ የቀሩ ነጋዴዎች እና አንዳንዶቹ ደግሞ መታሸጋቸውን ታዝበናል፡፡
የባሕር ዳር ከተማ ነዋሪና የሲሚንቶ ነጋዴ የሆኑት አቶ አዳሙ ጣእመው ጥናት ሳይደረግ ተግባራዊ የሆነው የዋጋ ተመን
ነጋዴዎችን ለኪሳራ እየዳረገ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊት በየቀኑ ከ200 ኩንታል በላይ ሲሚንቶ ሲሸጡ እንደነበር አቶ አዳሙ
አስታውሰዋል፡፡ “ሕገ ወጥ ደላሎችን አልፎ የሚመጣውን ሲሚንቶ በወጣለት የዋጋ ተመን መሸጥ ነጋዴውን አትራፊ እያደረገ
አይደለም” ነው ያሉት፡፡ በዚህ ምክንያት ማከማቻ ክፍላቸዉን ባዶ ለማድረግ መገደዳቸውን ነው ያስረዱት፡፡
አከፋፋዮችም ለቸርቻሪ ነጋዴዎች በአግባቡ የማከፋፈል ችግር እንዳለባቸው የተናገሩት አቶ አዳሙ የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት
ቢሮ አከፋፋይ ነጋዴዎችን መቆጣጠር፣ አቅርቦቱ እንዲጨምር መሥራትና በክልሉ የሲሚንቶ ፋብሪካዎችን በማስፋፋት ዜጎች
በግንባታ ዘርፍ ውጤታማ ሥራ የሚሠሩበትን ሁኔታ እንዲፈጠር ማስቻል አለበት ብለዋል፡፡
ወይዘሮ ዜናሽ ምሥጋናው ደግሞ በባሕር ዳር ከተማ በሲሚንቶ ማከፋፈል ሥራ ላይ ነው የተሰማሩት፡፡ ከፌዴራል ሲሚንቶ
አከፋፋይ ኤጀንሲዎች የሚረከቡትን ሲሚንቶ ለነጋዴዎች በያዙት ወረፋ በተመኑ መሠረት በማከፋፈል ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
በቀን በአማካይ ከሦስት እስከ አራት ሲሚንቶ የጫኑ ተሽከርካሪዎችን በማስገባት ለነጋዴዎች እያከፋፈሉ መሆናቸውን ነው
የነገሩን፡፡
ይሁን እንጂ ደንበኞች በሚጠይቁት ልክ እየቀረበ እንዳልሆነም ገልጸዋል፡፡ ነጋዴዎችም ከማከፋፈያው የወሰዱትን ሲሚንቶ
የንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ያወጣውን ተመን መሰረት አድርገው መሸጥ እንዳለባቸው ወይዘሮ ዜናሽ መክረዋል፡፡ የንግድና ገበያ
ልማት ቢሮም የወጣው ተመን ተግባራዊነቱን የመቆጣጠር ግዴታውን ሊወጣ እንደሚገባ ወይዘሮ ዜናሽ ጠቁመዋል፡፡
በአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ የሕጋዊ ስነ ልክ ባለሙያ ወይዘሮ እመቤት መላኩ በአማራ ክልል በየቀኑ በአማካይ ከ17
እስከ 20 ሺህ ኩንታል ሲሚንቶ የሚገባ መሆኑን ነግረውናል፡፡ የሲሚንቶ ነጋዴዎችም የሚቀርብላቸውን ሲሚንቶ የክልሉ ንግድና
ገበያ ልማት ቢሮ ባወጣው ተመን መሰረት መሸጥ እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
የሚቀርብላቸውን ሲሚንቶ በአግባቡ የማይሸጡ ነጋዴዎች ስለ አቅርቦት እጥረት ጥያቄ ማንሳታቸው ተገቢነት እንደሌለውም ነው
ባለሙያዋ የገለጹት፡፡ ቢሮው – በወጣው ተመን መሰረት የማይሸጡ ነጋዴዎችን መቆጣጠር ጀምሯል ያሉት ወይዘሮ እመቤት
በሕገ ወጥ ድርጊት ተሳትፈው የተገኙ ነጋዴዎች በሕግ እንዲጠየቁ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በፌዴራል ደረጃ የሚገኙ የሲሚንቶ አቅራቢ ኤጀንሲዎችም በክልሉ ለሚገኙ 28 አከፋፋዮች በየቀኑ በአግባቡ እንዲደርሱ እየተሠራ
መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ወይዘሮ እመቤት እንደነገሩን
• ደርባ ሲሚንቶ ከፋብሪካው በኩንታል 520 ብር ተገዝቶ በ572 ብር
• ዳንጎቴ ከፋብሪካው በኩንታል 525 ተገዝቶ 572ብር ከ50 ሣንቲም እየተሸጠ ነው፡፡ መንግሥት የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት በልዩ
ትኩረት እየሠራ መሆኑንም ወይዘሮ እመቤት ጠቁመዋል፡፡ ቢሯቸው ለሲሚንቶ ምርት የወጣውን የዋጋ ተመን ለማስተግበርም
በልዩ ዘመቻ እየተሠራ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
ዘጋቢ፡- አዳሙ ሽባባው
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በፌስቡክ https://bit.ly/2UwIpCw
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m




Previous articleየእንጨት ውጤቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት መዘጋጀቱን የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ ገለጸ፡፡
Next articleበኢትዮጵያ ከ20 ሚሊየን በላይ ትኩረት ያላገኙ የኅብረተስብ ክፍሎች የሥራ እድል ተጠቃሚ የሚሆኑበት አሠራር መፈጠር እንዳለበት የሥራ እድል ፈጠራ ኮሚሽን ገለጸ፡፡

Source link

The post በሲሚንቶ ግብይት የወጣውን የዋጋ ተመን ተግባራዊ ባላደረጉ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ first appeared on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.


Viewing all articles
Browse latest Browse all 13041

Trending Articles