
“ከፍያለው የኢትዮጵያውያኑ የዐዕምሮ ልዕልና ኢ-ሰባዊ ድርጊት ለመፈጸም እንዴት ቻለ”
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 28/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በንጹሃን ላይ የሚፈጸም ተደጋጋሚ ግድያ፣ መፈናቀልና የንብረት ውድመት
የሕዝቡን የአብሮነትና የመቻቻል እሴት እየሸረሸሩ መሆኑንና ቆም ብሎ በማሰብ የማስተካከያ ርምጃ መውሰድ እንደሚገባ
ምሁራን መክረዋል።
ምሁራኑ የሕዝብን እና የሀገረ መንግሥትን ቀጣይነት ያረጋገጡና በኢትዮጵያውያን የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ ውስጥ የነበሩ
ጠንካራ ማኅበራዊ መሠረቶች ትውልዱ ተቻችሎ እንዲኖር አስተዋዕጾአቸው ከፍተኛ እንደነበርም አስገንዝበዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከሚታወቅባቸው ወርቃማ ዕሴቶች መካከል ለዘመናት የዘለቀው ጠንካራ አብሮነት እና መቻቻል እንደሆነ
የሚናገሩት ምሁራኑ ኢትዮጵያውያን ጦርነትና ርሃብ የማይፈታቸው ሰብዓዊነት የነበራቸው ባለ ምሉዕ ሞራል ነበሩ ብለዋል።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን የማኅበረሰቡ የከፍታ መሰረት የነበሩ መልካም እሴቶች እየቀጨጩ ጎጠኝነት እና ኢ-ሰብአዊነት ከፍ
ብሏል፤ የነበሩ የአብሮነት፣ የመረዳዳት፣ የብዝኃነት እና የመከባበር ባህሎች በመገዳደል፣ በዝርፊያ እና በደባል ማንነቶች
ተተክተዋል ይላሉ ምሁራኑ።
በሀገሪቱ የሚታዩ የሕግ የበላይነት ጥሰት፣ አለመከባበር፣ ብዝኃነትን አምኖ አለመቀበል፣ የጎሳ የበላይነት አስተሳሰቦች እና
የመሳሰሉት ችግሮች በእሴት መሸርሸር የመጡ መሆናቸውንም በወሎ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን ጠቁመዋል።
በወሎ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለምአቀፍ ግንኙነት ትምሕርት ክፍል መምሕሩ ጀማል ሰይድ ማሕበራዊ መሠረቶች
በመሸርሸራቸው ባሕሉን፣ ሃይማኖቱን እና ሰብዓዊነቱን የማያከብር ሞራል አልባ ትውልድ መፈጠሩን አንስተዋል። በየቀኑ የሰው
ልጅ እንደ እንስሳ ሲታረድ፣ የፖለቲካ ዕውቀትና አመለካከት የሌላቸው ንጹሃን ሲገደሉ፣ ሲፈናቀሉ እንደዚሁም ሀብትና ንብረታቸው
ሲወድም የሕዝብ ስልጣን የያዙ አካላት በዝምታ መመልከታቸው፣ የሕግ የበላይነት ጥሰት የነገሰባት ሀገር እየተገነባች መሆኑ እና
ሕዝቡም ይህንን መጥፎ ድርጊት እየተለማመደው እንደሆነ የሚያመላክት ነው ብለዋል።
ከፍተኛ የኑሮ ውድነት፣ ጂኦ ፖለቲካዊ ውጥረት፣ ሀገራዊ የፖለቲካ ትኩሳት እና ውስጣዊ ችግሮች እየተስፋፉ ባለበት ጊዜ
ማኅበረሰባዊ መሠረቶች መሸርሸራቸውና በሀገሪቱ የሚታየው የሞራል ዝቅጠት እጅግ አስፈሪና አደገኛ መሆኑንም ተናግረዋል።
ልዩነት ተፈጥሯዊ በሆነባት ሀገር መቻቻል የግድ መሆኑን ያብራሩት አቶ ጀማል በዚህ ወቅት መቻቻል ማለት የሀገርን እና የሕዝብን
ሕልውና ማስቀደምና ፍላጎቶችን በቅደም ተከተል ማስቀመጥ እንደሆነ አስገንዝበዋል። ሀገርና ሕዝብን ለማስቀጠል አላስፈላጊ
እንቅስቃሴን መገደብ እንደሚገባም መክረዋል።
በወሎ ዩኒቨርሲቲ በፖለቲካል ሳይንስ ትምህርት ክፍል የሚያስተምሩት እንድሪስ ሁሴን በበኩላቸው በሀገሪቱ ለተፈጠረው ችግር
ትህነግ መራሹ ኢሕአዴግ ተጠያቂ ቢሆንም ከዚያም ወዲህ ተባብሶ መቀጠሉን አስታውቀዋል። “በሰላም ወጥቶ ለመግባት
እርግጠኛ መሆን አልተቻለም” ያሉት መምህሩ በኢትዮጵያ የተጋረጠውን አደጋ ለመቀልበስ የቀድሞ አባቶችን ዕሴት ማስቀጠል
እንደሚገባም መክረዋል።
መንግሥትም የደኅንነት መረቡን እና የጸጥታ መዋቅሩን አጠናክሮ የዜጎችን ደኅንነት የማስጠበቅ ግዴታውን በአግባቡ መወጣት
አለበት ብለዋል።
ይህ ሲሆን የኢትዮጵያውያን መልካም እሴቶች ይዳብራሉ። የመልካም ዕሴቶች መዳበርም ሰብዓዊነት ክብርን ያጎናጽፋል፣ ዜጎችም
በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲገቡ እድል ይፈጥራል። እንደ ምሁራኑ ማብራሪያም ሰብዓዊነትና የሀገር ህልውና ሲረጋገጥ
ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ትኩረት ያገኛሉ።
ዘጋቢ:- ደጀኔ በቀለ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በፌስቡክ https://bit.ly/2UwIpCw
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
The post “ከፍያለው የኢትዮጵያውያኑ የዐዕምሮ ልዕልና ኢ-ሰባዊ ድርጊት ለመፈጸም እንዴት ቻለ” first appeared on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.