
አዲሱን የአጠቃላይ ሥርዓተ-ትምህርት ወደ ተግባር ለማስገባት የሚያስችል ሰነድ ተዘጋጀ፡፡
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 09/2013 ዓ.ም (አብመድ) አዲሱን የአጠቃላይ ሥርዓተ-ትምህርት ለማሻሻልና የመጨረሻ ቅርጽ አስይዞ
ወደ ተግባር ለማስገባት የሚያስችል ሰነድ መዘጋጀቱን የትምህርት ሚኒስቴር ገለጸ።
ሰነዱን በባለድርሻ አካላት ለማስገምገም የተዘጋጀ አውደ ጥናት በቢሾፍቱ ከተማ ተካሄዷል።
በመድረኩ አጠቃላይ ሂደቱን ለባለድርሻ አካላት ያቀረቡት በሚኒስቴሩ የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅትና ምርምር ጄኔራል ዳይሬክተር
ዶክተር ቴዎድሮስ ሸዋርገጥ ናቸው።
ዶክተር ቴዎድሮስ በገለጻቸው ከነባራዊው የሀገሪቱ ትምህርት ዳሰሳዊ ጥናት በመነሳት ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ በተሰናዳው ፍኖተ
ካርታ ላይ በተደረገው ሰፊ ውይይት የትምህርት ፖሊሲ፣ የትምህርት ሕግ እና የ10 ዓመት መሪ ዕቅድ ተመቻችቷል።
የአሁኑ መድረክም የተዘጋጀውን ሥርዓተ ትምህርት የይዘት ፍሰትና ተፈላጊ የመማር ብቃት መለኪያ መርኃ ትምህርቱን በሀገር
ውስጥና ውጭ የብቃት አረጋጋጭ አካላት በማስገምገም በተገኘው ግብዓት በባለድርሻ አካላት የማፀደቅ ሥራ መሆኑን
ተናግረዋል።
የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ገረመው ሁሉቃ በበኩላቸው የዓለም ሀገሮች በስልጣኔ የቀደሙት ሥርዓተ ትምህርታቸውን
በየጊዜው በማሻሻል መሆኑን ጠቅሰዋል።
“ኢትዮጵያም ከነባራዊው ዓለም ሂደት ላለመለየት ሥርዓተ ትምህርቷን ለውጣለች” ብለዋል።
የሀገሪቱ ሥርዓተ ትምህርት ብዙ ችግሮች እንዳሉበት በጥናት መረጋገጡን ያወሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ለችግሩ መፍትሔ
ለማመንጨት ኢትዮጵያውያን ምሁራን አቅም መጠቀም እንደተቻለ ገልጸዋል። በዚህም መሰረት ከቅድመ መደበኛ ትምህርት እስከ
12ኛ ክፍል ሥርዓተ ትምህርት የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል።
መድረኩ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ አስተባባሪነትና ሌሎች አራት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የልህቀት ማዕከላት ተሳታፊነት ቀድሞ
በተሰበሰቡ ግብዓቶች መሰረት ሥርዓተ-ትምህርት ለማሻሻልና የመጨረሻ ቅርጽ አስይዞ ሰነዱ ወደ ተግባር እንዲገባ ለማፅደቅ
የተዘጋጀ መሆኑን አስረድተዋል።
በሰነድ ዝግጅቱ ከተሳተፉት ምሁራን መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስነ ዜጋና ስነምግባር ትምህርት ክፍል ኃላፊ ዶክተር
ተስፋዬ ጅማ እንዳሉት፤ አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት በቀድሞው የተጓደለውን በማስተካከል የሀገሪቱን ባህልና ልሳነ ብዝኃነት
መሰረት አድርጎ ተዘጋጅቷል።
የመማሪያ መጽሐፎቹ ሲዘጋጁ ትውልድን ለመገንባት ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲደረግባቸውም መገለጹን የዘገበው ኢዜአ ነው፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2HYJBLZ
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
The post አዲሱን የአጠቃላይ ሥርዓተ-ትምህርት ወደ ተግባር ለማስገባት የሚያስችል ሰነድ ተዘጋጀ፡፡ first appeared on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.